ከምርጫው በፊት አሜሪካ ” ስጋት አለብኝ” በሚል 300 የሚጠጉ የጥበቃ ልዩ ሃይል ማስገባት እንድትችል በቀጣታ ለጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ጥያቄ አቅርባ ነበር። የአዲስ አበባ ተባባሪያችን ስማቸውን ሳይጠቅስ ከፍተኛ ሃላፊ እንደነገሩት እንዳስታውቆ እንዳለው መንግስት ጥያቄውን ውድቅ አድርጎታል።
“አገሪቱ ሰላም ናት። እንደወትሮው ሰላም የማናስጠብቀው እኛ ነን” በሚል ጥያቄውን ውድቅ ሲያደርግ የከረረ ምልልስ ተደርጎ ነበር። በመጨረሻም መንግስት እንደማይሆን አስታውቆ ” ከፈለጋችሁ ምርጫው እስኪያልፍ ኤምባሲውን ጥላችሁ ውጡ” ብሎ ነበር። በመጨረሻ ግን ወታደሮች ሳይሆኑ ቁጥራቸው በውል ያልተገለጸ ሲቪል ዜጎቹን ማስገባቱ ታውቋል።
የኢትዮጵያ የፌዴራል መንግስት በትላንትናው ዕለት የተናጠል በሰብዓዊነት ላይ የተመሰረተ ተኩስ አቁም ካወጀ በኃላ የተለያዩ ሀገራት አስተያየታቸውን እየሰጡ ይገኛሉ።
እንግሊዝ
ብሪታንያ የኢትዮጵያ መንግስት ትግራይ ክልል ውስጥ የአንድ ወገን/ የተናጠል በሰብአዊነት ላይ የተመሰረተ የተኩስ አቁም ማድረጉን በደስታ እንቀበላለን ብላለች::
ለዚህም ሁሉም ወገኖች ዕውቅና እንዲሰጡ ፣ ግጭት ለማቆም እና ሕይወት አድን ሰብዓዊ ዕርዳታ በክልሉ በፍጥነት እንዲያደርስ ጠይቃለች::
ቻይና
የቻይና የኢትዮጵያን የተናጥል ተኩስ አቁም ጥሪ እንደምትደግፍ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ዋንግ ዌንቢን አማካኝነት አስታወቃለች፡፡
ቃል አቀባዩ “እኛ አትዮጰያዊያን የውስጥ ችግራቸውን በራሳቸው አቅም የመፍታት ጥበብ እንዳላቸው እናምናለን” ብለዋል፡፡
አረብ ኢምሬስት
የተባበሩት አረብ ኤሜሬቶች የፌደራሉ መንግሥት የተኩስ ማቆም ማወጁ ተቀባይነት ያለው ውሳኔ ነው ብላለች።
የተባበሩት አረብ ኤሜሬቶች የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ በኢትዮጵያ ግጭትን ለማቆም እና ፖለቲካዊ ስምምነት ላይ ለመድረስ ብቸኛው አማራጭ ፖለቲካዊ መፍትሄ ነው ነው ብሏል።
ቀጣይነት ያለው ሰላም እና መረጋገት ለማረጋገጥ በሕግ የበላይነት እና ሕገ-መንግሥታዊ ማዕቀፍ ውስጥ ገንቢ የሆኑ ውይይቶች ማድረግ ብቸኛው መንገድ ነው ሲል አክሏል።
ኳታር
ኳታር የፌዴራል መንግስት ያወጀውን የተኩስ አቁም ስምምነት እደግፋለሁ ስትል አሳውቃለች። ይህ ውሳኔ በሰላም ሂደቱ ላይ ትልቅ አስተዋፅኦ ይኖረዋል ብላለች።
UNICEF ያሰማው ክስ አሰማ
በትላንትናው ዕለት UNICEF ባወጣው ሪፖርት የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት አባላት በመቐለ ወደ ሚገኘው ቢሮ በመግባት የተቋሙን የሳተላይት መገናኛ ቁሳቁሶች በታትነዋል ብሏል።
የድርጅቱ ኃላፊ ሔንሪየታ ፎረ ይህ ድርጊት የተመድ ያለውን ያለመነካት መብት፣ ልዩ ጥበቃ እና ለሰብዓዊ ዕርዳታ የሚውሉ ቁሳቁሶች በዓለም አቀፍ ህግ የሚሰጣቸውን ጥበቃ ይጥሳል በማለት ኮንነዋል።
ሔንሪየታ ፎረ በትግራይ ግጭት ውስጥ የሚሳተፉ ወገኖች ለጦርነት ወቅት ሕግጋት እንዲገዙ እንዲሁም የግብረ ሰናይ ተቋማትን እንዲያከብሩ ጠይቀዋል። እስካሁን ድረስ በUNICEF ለቀረበው ክስ የኢትዮጵያ መከላከያ የሰጠው መልስ የለም። መንግስት ምላሽ ባይሰጥም ምስክሮች በመሳሪያው ትህነግ እንደሚጠቀምበት በቂ ማስረጃ አለ። ዩኒሴፍም ያውቃል ሲሉ ተናግረዋል።
የዩኒቨርሲቲ ተማሪ ወላጆች እና ከትግራይ ውጭ ያሉ ቤተሰቦች ጭንቀት :
በትግራይ ክልል ባሉ ዩኒቨርሲቲዎች ልጆቻቸውን ልከው የሚያስተምሩ ወላጆች በክልሉ እየሆነ ስላለው ጉዳይ በእጅጉ ተጨንቀዋል። በመቐለ ጨምሮ በሌሎችም የትግራይ ክልል ከተሞች ሙሉ በሙሉ ኔትዎርክ ተቋርጧል። የልጆቻቸውን ድምፅ መስማት ፣ ያሉበትን ሁኔታ ማወቅ አልቻሉም።
በሚመለከተው የመንግስት አካላት እስካሁን የተባለ ነገር የለም፤ ቲክቫህ ኢትጵያ ተማሪዎች ስላሉበት ሁኔታ በቲክቫህ ዩኒቨርሲቲ ገፁ አማካኝነት ለማጣራት ስራዎችን እየሰራ ነው።
በሌላ በኩል ከትግራይ ውጪ የሚኖሩ ትግራይ ክልል የሚኖሩ ቤተሰቦቻቸውን ግኘት እንዳልቻሉ ጠቁመዋል። ይህም ከፍተኛ ጭንቀት እንዳሳደረባቸው ገልፀዋል። ቤተሰቦቻቸው ስላሉበት ሁኔታ በተደጋጋሚ ስልክ ቢሞክሩም አይሰራም።
ከዚህ ቀድም የትግራይ ግጭት ሲጀመር ኔትዎርክ ለረጅም ጊዜ ተቋርጦ ግንኙነት ማድረግ አልተቻለም በኃላም የፌዴራል መንግስት ትግራይን ሲቆጣጠር ተመልሶ ነበር።
ትህነግ ወደ መቀለ እንደገባ የስልክ መስመር መቁረጡን እማኞች እየገለጹ ሲሆን ለጊዜው ከተማ የገቡት የቀድሞ የኢንሳ ሃላፊ የዩኒሴፍን መገናኛ እንደሚጠቀሙ አመልክተዋል።
አምነስቲ ኢንተርናሽናል
አምነስቲ ኢንተርናሽና የምስራቅ አፍሪካ ምክትል ዳይሬክተር ሳራ ጃክሰ አምነሲቲ ኢንተርናሽናል በትግራይ ያሉ ሲቫ ዜጎችን ደህንነት እንደማያሳስበው ገልፀዋል።
ላለፉት ወራት በትግራይ በነበረው ውጊያ፣ በሁሉም ወገኖች በተፈፀሙ ከፍተኛ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ፣ የጦር ወንጀሎችን በመቋቋም ያሳለፉ የትግራይ ሲቪል ዜጎች ደህንነት አሁንም አምነስቲን እንደማያሳስበው አሳውቀዋል።
የኢትዮጵያ ጦር የያዛቸውን ቦታዎች እየለቀቀ መሆኑን እና የትግራይ ክልል ኃይሎች ቦታዎችን እየተቆጣጠሩ መሆኑን ያነሱት ሳራ ጃክሰን በዚህ ወቅት ለዜጎች የሚደረገው ጥበቃ ከሁሉም በላይ መሆን አለበት ብለዋል።
አክለውም ፥ “ሁሉም ወገኖች ተጨማሪ የጭፍጨፋ እና የጦር ወንጀሎች እንዳይፈፀም እንዲከላከሉ ጥሪ እናቀርባለን” ብለዋል። በወታደሮች እና ሚሊሻዎች የበቀል ጥቃቶች እንዳይፈፀሙ በማረጋገጥ እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
በተጨማሪ ፥ ሁሉም ወገኖች ለሲቪል ዜጎች ያልተገደበ የሰብአዊ እርዳታ ተደራሽ እንዲሆን ማረጋገጥ አለባቸው እንዲሁም በአሁኑ ወቅት የኢንተርኔት ፣ የህትመት ወይም የብሮድካስት ሚዲያ ስለሌለ ሙሉ የግንኙነት ተደራሽነትን ለመመለስ መስራት አለባቸው ብለዋል።
አምነስቲ በሁሉም ወገኖች በትግራይ ሲቪል ዜጎች ላይ የበቀል የበቀል እርምጃ ሊወሰድ ይችላል የሚል ስጋት አለ ብሏል ( – ወደ ኋላ የሚመለሱ የመከላከያ ወታደሮች ፣ በአጎራባች አማራ ክልል እና በኤርትራ ኃይሎች እና በTDF (የህወሓት ታጣቂ ኃይሎች)ን በማንሳት።
የአሜሪካ ትግራይ ክልል ያለውን ሁኔታ በቅርበት እየተከታተለች እንደምትገኝ ገልፃለች።
አሚሪካ ይህን ያለችው ዛሬ በአዲስ አበባ ኤምባሲዋ ባወጣችው መግለጫ ነው አሜሪካ በአሁን ሰዓት ከመቐለ የሚነሱና ወደ ከተማዋ የሚደረጉ በረራዎች ቆመዋል፣ በረራዎች መቼ እንደሚጀምር አይታወቅም ብሏለች።
በተጨማሪ ወደ መቐለ የሚወስዱ መንገዶች ተዘግተዋል፣ የህዝብ ማመላለሻ ተሽከርካሪዎች አገልግሎት እየሰጡ አይደለም፣ ስልክ ግንኙነት ተቋርጧል ብላለች።
ቅድሚያ ለዜጎቿ እንደምትሰጥ የገለፀችው አሜሪካ በትግራይ የሚገኙ ዜጎቿ የአካባቢ ሚዲያዎችን እንዲከታተሉ ፣ የቆንጽላ መልዕክቶችን እና የኤምባሲዉን ማህበራዊ ሚዲያ አንዲከታተሉ መልዕክት አስተላልፋለች። ዜጎቿ አስፈላጊውን ጥንቃቄ አንዲያደርጉ አሳስባለች።
የአቶ ጌታቸው ረዳ አስተያየት
የኢትዮጵያ ፌዴራል መንግስት እጅግ በጥብቅ ከሚፈልጋቸው የቀድሞ የትግራይ ገዢ ፓርቲ ህወሓት አመራሮች መካከል አንዱና ዋነኛው የሆኑት አቶ ጌታቸው ረዳ ለሮይተርስ ዜና ወኪል በሰጡት ቃል ፥ መቐለ 100% በቁጥጥራችን ስር ነች ብለዋል። የቀድሞው መንግስት ወደስራው ተመልሷልም ሲሉ ገልፀዋል።
በሌላ መረጃ አቶ ጌታቸው ረዳ የትግራይ ኃይል ፥ ኤርትራ እና አማራ ክልል ውስጥ ሊገባ እንደሚችል ዛሬ ከሰዓት ለሮይተርስ በሰጡት ቃል ገልፀዋል። አቶ ጌታቸው “አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ የ “ጠላት” ኃይሎችን ለማሳደድ/የውጊያ አቅም ለማዳከም ወደ ኤርትራ እና አማራ ክልል እንገባለን” ብለዋል። አማራ ክልል በበኩሉ ሞክሩት ሲል ዝግጁ መሆኑንን ጠቅሶ መግለጫ አውጥቷል።
የፀጥታው ም/ቤት ስብሰባ ጥሪ
የተባበሩት መንግሥታት የጸጥታው ምክር ቤት በትግራይ ጉዳይ አስቸኳይ ስብሰባ እንዲጠራ ጥሪ ቀርቦለታል። የጸጥታው ምክር ቤት አስቸኳይ ስብሰባ እንዲጠራ የጠየቁት አሜሪካ፣ ዩናይትድ ኪንግደም እና አየርላንድ መሆናቸውን AFPን ዋቢ አድርጎ ቢቢሲ ዘግቧል። ለAFP ቃላቸውን የሰጡ ዲፕሎማቶች እንዳሉት ከሆነ የተመድ የጸጥታው ምክር ቤት በትግራይ ጉዳይ የፊታችን አርብ ሊወያይ ይችላል።
አገራቱ አስቸኳይ ስብሰባ እንዲካሄድ የጠየቁት የፌደራሉ መንግሥት ጦር መቀለን ለቅቆ መውጣቱን ተከትሎ የትግራይ ኃይሎች የክልሉን መዲና መቆጣጠራቸው ከተሰማ በኋላ ነው።
ጥንቅሩ @tikvahethiopia ሲሆን ዝግጅት ክፍሉ መረጃ ጨምሮበታል።