ቻይና በኢትዮጵያ ያላት የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት መጠን 3 ነጥብ 3 ቢሊዮን ዶላር መድረሱ ተገልጿል።
ይሄም በአፍሪካ የመጀመሪያው ደረጃ ላይ የሚቀመጥ መሆኑ ተነግሯል። የኢትዮጵያና ቻይና የኢንቨስትመንት ፎረም ትናንት በቤጂንግ ተካሂዷል።
ፎረሙን ያዘጋጁት በቤጂንግ የኢትዮጵያ ኤምባሲ እና የቻይና ኢንቨስትመንት ፕሮሞሽን ኤጀንሲ በጋራ በመሆን ነው።
በፎረሙ ላይ በገንዘብ ሚኒስትር አቶ አህመድ ሽዴ የተመራ ልዑክ የፕሮሞሽን ኤጀንሲው ዳይሬክተር ጀነራል ሊዩ ዲያንሱን እና ከ62 የቻይና ኩባንያዎች የተወጣጡ ከ180 በላይ ስራ አስፈጻሚዎች፣ባለቤቶች እና ባለሙያዎች ተሳትፈዋል።
የኢንቨስትመንት ፎረሙ በወንድማማችነት ላይ የተመሰረተውን የኢትዮጵያ እና ቻይና ግንኙነት ይበልጥ ለማጠናከር ወሳኝ መሆኑን የገንዘብ ሚኒስትሩ ገልጸዋል።
የሁለቱ አገራት ግንኙነት በመልካም እና አስቸጋሪ ወቅቶችም በተመሳሳይ ወዳጅነት የቀጠለ ነው ብለዋል።
የኢትዮጵያ ልማት አጋር የሆነችው ቻይና ለኢትዮጵያ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ እድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቷን ተናግረዋል።
የቻይና የመንግስት እና የግል ኩባንያዎች በኢኮኖሚና መሰረተ ልማት ዘርፎች የገነቧቸው ፕሮጀክቶች የኢትዮጵያውያንን ሕይወት በተጨባጭ ለውጥ ከማምጣታቸው ባሻገር ኢትዮጵያን ተወዳዳሪ እና ሳቢ የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት መዳረሻ ማድረጉን ነው ሚኒስትሩ ያስረዱት።
የቻይና ኢንቨስትመንት ፕሮሞሽን ኤጀንሲ ዳይሬክተር ጀነራል ሊዩ ዲያንሱን በበኩላቸው ኢትዮጵያ እና ቻይና በንግድ ፣ በኢንቨስትመንት ፣ ጤና እና ሌሎች መስኮች ፍሬያማ ግንኙነት እንዳላቸው ገልጸዋል።
እ.አ.አ 2022 ቻይና በኢትዮጵያ ያላት የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት መጠን 3 ነጥብ 3 ቢሊዮን ዶላር መድረሱንና ይሄም በአፍሪካ የመጀመሪያው ደረጃ ላይ እንደሚቀመጥ ተገልጿል።
የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር ለሊሴ ነሜ የኢትዮጵያን የኢንቨስትመንት አማራጮች እና እድሎች እንዲሁም መንግስት በዘርፉ እያከናወናቸው የሚገኙ ስራዎች የተመለከተ ገለጻ አድርገዋል።
የቻይና ኩባንያዎች ኢትዮጵያን ቀዳሚ የኢንቨስትመንት መዳረሻ እንዲያደርጉም ጥሪ አቅርበዋል።
በፎረሙ ላይ በተካሄደው የፓናል ውይይት የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ሁኔታ እና ቀጣይ የኢኮኖሚ ትንበያ፣ የኢትዮጵያ መንግስት ኢኮኖሚውን ለማሳደግ እየወሰዳቸው ያሉ የማሻሻያ እርምጃዎች፣ አገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ፣ አዲስ የተከፈቱ የኢንቨስትመንት ዘርፎች እና የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ የተመለከቱ ሀሳቦች ተነስተዋል።
በፎረሙ ላይ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዢ አቶ ማሞ ምህረቱ፣ የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር እዮብ ተካልኝ እና ሌሎች የመንግስት የስራ ኃላፊዎች መገኘታቸውን የኢዜአ ዘገባ ያመለክታል።