በአሜሪካ የባርነት ጭቆና በሕግ ሰፍኖ በነበረበት ወቅት “ባሪያ” ተብለው የሚጠሩት እንደ ዕቃ እንጂ እንደ ሰው እኩል አይቆጠሩም ነበር። ይህም ማለት አንድ ባሪያ አንደ አንድ ሙሉ ሰው አይቆጠርም ነበር። ወይም አነሱ ሙሉ ከሚሉት ከአንድ ሰው በታች ነበር። “ባሮች” በደቡቡ ክፍል በርካታ በመሆናቸውና ቁጥራቸውም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ በመምጣቱ የደቡቡ አስተዳዳሪዎች ለጥቅማቸው ሲሉ አንድ 3/5ኛ የተባለ ስምምነት እንዲታወጅ አደረጉ።
(ተፈራ መንግስቱ)
ከሶስት አመት በፊት ሚሪላንድ አንድ ቆንጆ ምግብ ቤት ውስጥ አራት የአንድ ዩቲዩብ ቡድን ተሰባስበው ጥሬ ይቆርጣሉ። ቶሎ ቶሎ አያዘዙ ይጎነጫሉ። ድንገት ሁለት ጠና ያሉ አህቶች ከጎኔ ይቀመጡና የሚፈልጉትን ያዛሉ። ዞር ሲሉ እነዚህን የዩቲዩብ ጋንጎች ያይዋቸዋል። ከዛም ኣንደኛዋ ብድግ ብለው “ አፈር ብሉ፤ ደም ጠጡ። አዛ አገር እያባላችሁ፣ ደም አያፋሰሳችሁ አዚህ ቁርጥ ትበላላችሁ። ወላዲት አምላክ — እመቤቴ ” እርግማናቸውን ኣይናቸውን አያፈጠጡ አወረዱባቸው። አነሱ ወይ ፍንክች፣ ያዛሉ —- ሰው ወዶና ፈቅዶ “ ሸቀጥ” ሆነና ተነገደበት!!
በአሜሪካ የባርነት ጭቆና በሕግ ሰፍኖ በነበረበት ወቅት “ባሪያ” ተብለው የሚጠሩት እንደ ዕቃ እንጂ እንደ ሰው እኩል አይቆጠሩም ነበር። ይህም ማለት አንድ ባሪያ አንደ አንድ ሙሉ ሰው አይቆጠርም ነበር። ወይም አነሱ ሙሉ ከሚሉት ከአንድ ሰው በታች ነበር። “ባሮች” በደቡቡ ክፍል በርካታ በመሆናቸውና ቁጥራቸውም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ በመምጣቱ የደቡቡ አስተዳዳሪዎች ለጥቅማቸው ሲሉ አንድ 3/5ኛ የተባለ ስምምነት እንዲታወጅ አደረጉ።
ጉዳዩ ለባሪያዎቹ ታስቦ ሳይሆን ለፖለቲከኞቹ የግል ጥቅም ማስፈጸሚያ ነበር። እንደሚታወቀው በአሜሪካ የምክርቤት መቀመጫ የሚወሰነው በሕዝብ ቁጥር ነው። ታዲያ ለዚሁ የውክልና ምርጫ ባሪያዎች እንዲቆጠሩ ከተደረገ ባሪያዎች ከነጮች እኩል ሰው ተብለው ድምጽ ሊሰጡና እንደ ንብረት ወይም ሸቀጥ መቆጠራቸው ቀርቶ መብታቸው ሊከበር ነው። ስለዚህ አማራጭ ሆኖ የተገኘው በታሪክ “የ3/5ኛ ስምምነት” የሚባለውን በሕገመንግሥቱ ውስጥ በማሻሻያነት እንዲካተት ማድረግ ነበር።
በመሆኑም በ1787 በተደረገው ስምምነት መሠረት 5 ባሪያዎች እንደ 3 ሙሉ ሰው እንዲቆጠሩ በሕግ ተደነገገ። ይህ በደቡብ ላሉትና አናሳ ቁጥር ለነበራቸው ነጮች የበለጠ የምክር ቤት ወንበርና የመሳሰለውን የፖለቲካ ጥቅም አስገኘላቸው። ባሪያዎቹ ግን በዚህ መልኩ ቢቆጠሩም በፖለቲካ የመሳተፍ፣ ድምፅ የመስጠት አንዳችም መብት አልነበራቸውም። ይህን ለምን ዛሬ ላይ አነሳሁት? “ሰው” የሚባለው ክቡር ፍጡር በፖለቲካ ቁማርተኞች ጥቅምና ፍላጎት ሲባል አንዴት “ሸቀጥ” አንደሚደረግ ለማሳየት ነው።
ሰው ወደ ገበያ ሲወጣ ሸቀጥን ይገዛል። ሰው ሸቀጥን ይገዛል ሲባል ሸቀጥ ለሰው መገልገያ የሚውል በገንዘብ የሚለወጥን ነገር አንደፍላጎቱ ይጠቀምበታል ማለት ነው። ምንም ነገር በገንዘብ ከተለወጠ ሸቀጥ ሆነ ማለት ነው። ሰው ራሱ የገንዘብ ማስገኛ ከሆነ ከሰውነት ወርዶ ሸቀጥ ሆኗል ማለት ነው።
በአገራችን ተጨባጭ ሁኔታ ዛሬ በዩቲዩብ አለም ያለው እምነት “ የሰው ልጅ ሸቀጥ ነው” በሚል መርህ የተመሰረተ ነው። ይህን “ሰው” የተባለ ክቡር ፍጡር ወደ ሸቀጥነት አውርዶ የሚያይ አለም ነው። ሰውን ያክል ፍጡር ይሙት፣ ይታረድ፣ ይጨፍጨፍ፣ ለአብዛኞቹ የዩቲዩብ ገበያተኞች ሲሳይ አንጂ ሃዘን የማይሆነው ከዚሁ “የሰው ልጅ ሸቀጥ ነው” ከሚለው መርሃቸው የተነሳ ነው።
የመንግስትን ግብር አስከፋዮችና ህግ አስፈጻሚዎች ነሆለልነት አንዳለ ሆኖ እርስዎ፣ አንተ፣ አንቺ፣ እኛ፣ ሁላችንም ይሉኝታና ሃዘኔታን አንክት አድርጎ በበላው የመርዝ ማሰራጫ የአገራችን የዩቲዩብ ነብሰ በላዎች ምድብ ተደልድለን አንደሆነ ያውቃሉ? ይህን ጥያቄ ለመመለስ የሚከተሉትን ነጥቦች ያስሉልኝ።
አንዱ ዋሽንግተን ዲሲ የቸኮለ ባልደረባውን ያገኘዋል። ረጋ ብሎ ቡና አንዲጠጡ ሲጠይቀው ስም ጠርቶ “ ማታ ማታ ቁጭ ብዬ ዛሬ ምን አለ ላይ ስተነትን ልጆቼ አየሰሙ ተጨነቁ። የሚነሳው ጉዳይ ከባድ ስለሆነ ሚስቴም ጤና አይሰማትም። በተለይ የልጆቼ ሰላም ተናግቷል። ምድር ቤትህን አከራየኝ ብሎ አከራየሁት። ምድር ቤት ስለሆነ ኢንተርኔት አየተቆራረጠበት ስላስቸገረው —-” ብሎ የኢንተርኔት ኣቅሙን የሚጨምሩ ባለሙያዎች መቅጠሩን ነገሮኝ ተከፈተለከ። ልብ እንበል አሱ በሚረጨው መርዝ ቤተሰቦቹ ታውከዋል። ልጆቹ ተጨንቀዋል። አንተ፣ አንቺ፣ አናንተ ክሊክ ባደረጋችሁት ልክ ሳንቲም የሚለቅመውና ከዚሁ ሳንቲም ቤተሰቦቹን የሚቀልበው፣ የሚያስውበው፣ የሚያቀማጥለው “ ተንታኝ” ወደ ኣገርቤት የሚረጨው መርዝ ለሱ ቤተሰቦች አይስማም። ታዲያ በዚህ ቅጥረኛ ጭንቅላት ከሱ ቤተሰቦች ሌላ የሚጸቅልባቸው “ሰዎች” ምኑ ናቸው?
ይህን እንደ ማሳያ ካነሳሁ ዋናውን ጭብጤን ጥያቄ በማከል ላቅርብ። በዛሬዋ ኢትዮጵያ ወቅታዊ ሁኔታ ማንም ይሁን ማንም ከላይ የተጠቀሱትንም ሆነ ዝም ብለው አንደቆርቆሮ የሚጮሁትን የዩቲዩብ ማሰራጫዎች ክሊክ ባደረገ ቁጥር “ ወገኖቼን ጨፍጭፉ፣ አስጨፍጭፉ” አንደማለት እንደሚቆጠር እንረዳለን? መረዳት ብቻ ሳይሆን የገንዘብ ምንጭ ለመሆን የተስማማን “ ሸቀጦች” አንደሆን ይገባናል? ምክንያቱም የገንዘብ ምንጭ ሆነናልና። አለያም በሁለት ድርጅቶች መካከል በተደረገ ግብይት ውስጥ ገንዘብ ለማምረት የተመረጥን ቁሶች ከመሆን አናልፍም።
ጥያቄው በርጋታ የሚመለስ ነው። ጥያቄው ራስንና ሰውነትን በማክበር የሚሰላ ነው። ይህ ከሰውነት ወርዶ “ቁስ” የመሆን ውሳኔ አያንዳንዱ በግል የሚወስነው ሲሆን አውሮፓና አሜሪካ የሚኖሩ የዚህ ገበያ ተመራጮች በመሆናቸው ሸቀጥነታቸው ወይም ለዩቲዩብ ገበያ ትርፋማነታቸው የበዛ፣ ተፈላጊነታቸው የጎላ የሚመደቡበት የግብይት ደረጃ አጅግ የወረደ ነው።
በውጭ አገር የሚኖሩ ዜጎች ፅዳት ሰርተው፣ ቆሻሻ ጠርገውና ኣድካሚ ስራ ሰርተው ያላገኙትን ሃብት ቁጭ ብለው መርዝ የሚረጩ ባንዳና የባንዳ ተላላኪዎች ያገኛሉ። እነዚህ ተላላኪዎች በጓሮ ከሚከፈላቸው በላይ፣ ዜጎችን “ሸቀጥ” አድርገው በንጹሃን ድምና አልቂት ላይ አየተረማመዱ ገንዘብ ሲያመርቱ ማላዘኛቸው ወገን መስሎ ማላዘን ነው።
እኒህ የዩቲዩብ አርበኞች በባንዲራ፣ በኢትዮጵያና በዘራቸው ካባ ውስጥ ተጠቅልለው በአስመሳይነት ቀውስ ሲያራቡ፣ እየተናበቡ የቀውስና የእልቂት ድንኳን ሲተክሉ “አገር ወዳድ ከሆናችሁ አስኪ ግብር የከፈልችሁበትን ደረሰኝ” ብሎ የሚጠይቅ የለም።
ይህንን ጽሁፍ ሳዘጋጅ፣ ለማጣራት አንደሞከርኩት በየትኛውም ደረጃ፣ በአገር ውስጥም ይሁን በውጭ የሚንቀሳቀሱ የዩቲዩብ ባለቤቶች ስሙኒ ግብር ከፍለው አያውቁም፤ ገቢያቸውንም ለማሳወቅ ፈቃደኛ የሆኑ የሉም። የኣንድ ኣገር ወዳድ ዋና መመዘኛው ግብር መክፈል መሆኑ ልብ ይሏል። በኣገራችን የቀውስ ጠማቂዎች በኢትዮጵያ ስም ቢምሉም ዋናውን የምህላ ማጽኛ አገራዊ ግዴታ ይረግጡታል። በተሰበሰቡ መረጃዎችና ባለኝ የግል እውቂያ አግራቸውን አገር ቤት ያደረጉ አስመሳይ አላዛኞች በሞትና በደም ላይ አየደነሱ የሚሰበስቡትን ገንዘብ የሚያስቀምጡት አውጭ ኣገር ነው። ቀን ጠብቀውና ኣድብተው እያላዘኑ ዶላር የሚለቅሙትም በተመሳሳይ ሃብታቸው በውጭ ባንክ ለመሆኑ የዚህ ሽሁፍ አቅራቢ ምስክር ነው።
ነሆለሉ ግብር ሰብሳቢ አካል ቡና በጤናዳም የምትሸጠውን አየተከታተለ ቀረጥ ሲለቅም፣ ገቢን መሰወር ወንጀል አንደሆነ የሚደነግገውን የአገሪቱን ህግ ጠቅሶ የዩቲዩብ መዝባሪዎችን ግብር ለምን አንደማያስከፍል ለዚህ ጽሁፍ አቅራቢ ግራ ነው። በሌሎች አገሮች ገቢን ሪፖርት ማድረግ የተለመደ አሰራር ሆኖ ሳለ፣ በውጭ ያሉት በዚሁ አግባብ አንደሚዳኙ አየታወቀ ዝምታው መንግስትን “ አበጃችሁ” አንደሚላቸው ያስቆጥርበታል የሚል ግምት ያስወስዳል።
ሲጀመር “ጎ ፈንድ” በሚባለው ዘመናዊ ልመና ኪስ የሚያወልቀው የዩቲዩብ ንግድ፣ ለቤሰሰብ ለመናን፣ ባንዳነትን፣ ህሊና ቢስነትን፣ የስብእና ስብራትን ከማውረስ ውጭ ሌላ ትርጉም እንደማይኖረው ኣድሮ የሚታይ ነው። ዛሬ መረጃ አየር ላይ ከዋለ ከሃብት ይልቅ ዘር ማንዘር ቀድሞ የሚወርሰው ቀርስ አንደሆነ መረዳት የተሳናቸው ከርሳሞች ለሆዳቸውና ለተቀጠሩበት የክህደት ውል ሲሉ ኢትዮጵያ ላይ የሚርመሰመሱባት አኛው ስለፈቀድንላቸው ነው።
ከዚህ በታች ያለው የዩቲዩብ ገቢ አንድም ሳንቲም ግብር ያልተከፈለበት ነው። ነሆለሉ ግብር ሰብሳቢው አካል ጠልቆ ገብቶ በመመርመር ግብር ማስከፈልን፣ ከከፋያቸው ጋር መረጃ በመቀያየር የተሰወረርውን የገቢ መጠን የማወቅና አውቆም በግብር ስወራ ወንጀል ለመጠየቅ “ወደፊት” ሊል ይገባል።
ማሳሰቢያ፦ ይህ ፅሁፍ ለሀገራችን ሰላምና ዴሞክራሲ መስፈን የላቀ አስተዋፅኦ እያደረጉ የሚገኙትን የዩቲዩብ ቻናሎችን አይመለከትም። በዚህ ፅሁፍ ላይ አስተያየትም ሆነ የተለየ ሀሳብ ማቅረብ ለምትፈልጉ ተቀብለን የምናስተናግድ መሆኑን እንገልፃለን።
ከአገር አማን መጽሄት የተወሰደ