በባሕር ዳር ከተማ ውስጥ የሽብር ጥቃት ለመፈፀም የተንቀሳቀሱ አካላት በቁጥጥር ስር መዋላቸውን የአማራ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን ገልጿል።
የአማራ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን የሚዲያና ኮሙኒኬሽን መምሪያ ኃላፊ ኮማንደር መሰረት ደባልቄ በሰጡት መግለጫ እንደገለፁት “በሀገሪቱና በክልሉ ሕግ ለማስከበር እየተንቀሳቀስን እንገኛለን” ብለዋል፡፡
ሰኔ 20 ቀን 2014 ዓ.ም ምሽት ኅብረተሰቡን ለማሸበር ያለመ ወንጀል ለመፈፀም የፈለጉ ቀሪ ኀይሎች በባሕርዳር ከተማ በአራት ቦታዎች ላይ ቦንብ እንዳፈነዱ ገልጸዋል።
ፖሊስ ከሕዝብ ጋር በመቀናጀት ባደረገው ክትትልም ወዲያውኑ 6 ተጠርጣሪዎችን በቁጥጥር አውሏል ነው ያሉት።
የተጠርጣሪዎች ቤት በሚፈተሽበት ወቅትም 2 ቦንብ፣ 3 ብሬን መሳሪያ እና 3 ሺህ 700 ጥይት፣ አንድ ስናይፐርና 500 ጥይት እንዲሁም በቀጣይ ተመሳሳይ የሽብር ወንጀል ለመፈፀም የያዙትን እቅድና መመሪያ ፖሊስ መያዙን ኮማንደር መሰረት ተናግረዋል።
በዚሁ ምሽት ከዚሁ ሽብር ጋር ግንኙነት ያላቸው 14 ተባባሪ አካላት በቁጥጥር ስር ውለው የክልልና የፌዴራል የፀጥታ አካላት ምርመራ እያደረጉ ይገኛሉ ሲል አሚኮ ዘግቧል።