ሰሞኑንን አቶ ጌታቸው ከአዲስ አበባ መልስ በሰጡት መግለጫ ካነሱዋቸው ጉዳዮች ይልቅ የተዘለሉት ጉዳዮች ቁልፍ መሆናቸው ተሰምቷል። ትህነግ ሁለት አማራጭ ተቀብሎ እንደሄደ ነው የተሰማው። ” እየከፋፈሉን ነው” የሚለው የአቶ ጌታቸው ገለጻም ከዚሁ ጋር የሚያያዝ እንደሆነ ተመልክቷል። ምርጫ ማነቆ እንደሆነ ተሰምቷል።
ራሱን የትግራይ ህዝብ ነጻ አውጪ ግንባር /ትህነግ የሚለው የትግራይ ክልል ድርጅት፣ የክልሉ ጊዚያዊ አስተዳደር፣ የሰራዊቱ መሪዎች ባሉበት ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ደግሞ ከሙሉ ካቢኒያቸው ጋር ሆነው ግምገማ ማካሄዳቸው ይታወሳል።
የቅርብ የመረጃ ምንጮች እንዳሉንና አስቀድመን እንደዘገብነው በተለይ አቶ ጌታቸው በጥብቅ ነው የተገመገሙት። በጠቅላይ ሚኒስትር አብይ የተሾሙት አቶ ጌታቸውና የጊዜያዊ አስተዳደሩ አካላት ስራ ከጀመሩ አንስቶ ሪፖርት አላቀረቡም። 37 ቢሊዮን ብር የወጣበትን ስራ አስመልክቶ መረጃ ሰጥተው አያውቁም።
አቶ ጌታቸው ደጋግመው እንደሚሉት 270 ሺህ ወታደር ካም አስቀምተው ከከልሉ በጀት እየቀለቡ ነው። ” የፕርቲቶሪያው ስምምነት ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ ካልሆነ ሰራዊት አንበትንም” ያሉት አቶ ጌታቸው በግልጽ ባይናገሩም የክልሉን በጀት ለሰራዊቱ ቀለብና ክፍያ መጠቀም እንደሚቀጥሉበት ነው ያስታውቁት።
በዚህ መነሻና በተለያዩ ጉዳዮች ሪፖርት ያላቀረቡት አቶ ጌታቸው “ካልቻልክ ልቀቅ” የሚል ማስጠንቀቂያ እንደሰጣቸው መረጃ ደርሶናል። ካሁን በሁዋላ ለፊደራል መንግስቱ በአግባቡ ሪፖርት የማያቀርቡ ከሆነ እርምጃ እንደሚወሰድም በጥብቅ ተገልጿል። ለዚህ ይመስላል አቶ ጌታቸው ” ሪፖርት አቅርበን ተመልሰናል” ያሉት።
ዋናው የተነሳው የትህነግ የዕውቅና ጉዳይ ሲሆን አግባቡ አቶ ጌታቸው ባሉት መልኩ የተስተናገደ አልነበረም። የዜናው ሰዎች እንዳሉት የዕውቅናው ጉዳይ በህጉ መሰረት እንደሚከናውን ጠቅሰው ብልጽግና ለትህነግ ሁለት አማራጭ አስቀምጧል። አንደኛው ትህነግ ብልጽግናን እንዲቀላቀል፣ አለያም ብልጽግና ባሻው መልኩ በትግራይ የራሱን የፖለቲካ ስራ መስራት እንደሚጀመር ተገልጾ ምርጫውን እንዲያሳውቅ ነበር የቀረበው አማራጭ።
ለጊዜው እሺ ወይም እምቢ የሚል ምላሽ ባይሰጡም የትህነግ ሰዎች መንግስት ትግራይን እንደቀድሞ ለትህነግ ብቻ አሳልፎ በሞኖፖሊ እንደማይሰጥ በይፋ ገልጿል። የዜናው አቀባዮች እንደሚሉት ይህ ሲገለጽ ” መንግስት በትግራይ ሌላ ዝግጅት አድርጓል” በሚል የጥርጣሬ ጥያቄ ተነስቷል። እንደውም በትግራይ የሚንቀሳቀሱ ተቃዋሚዎች ውስጥ ውስጡ የጨረሱት ጉዳይ እንዳለም እየተሰማ ነው። አስተያየት የጠየቅናቸው “ትህነግ አሁን ባለበት እድፍ ምርጫ ላይ ለመቅረብ ህዝቡን አደባባይ ወጥቶ ምን ይላል” ሲሉ ይጠይቃሉ። እነዚህ ወገኖች እንደሚሉት ትህነግ ብልጽግናን ከመቀላቀል ውጭ አንዳችም አማራጭ የለውም።
ስለቀረበለት ምርጫ ለህዝብ ትንፍሽ ያላለው ትህነግ ምርጫው የሞት ሽረት አጣብቂኝ ሆኖበታል። እነ ጻድቃን “ብልጽግናን እቀላቀል” የሚል አቋም ሲንይዙ፣ እነ ደብረጽዮን ደግሞ “አይሆንም ምርጫ ቢደረገም እናሸንፋለን ራሳችንን ችለን እንቀጥል” የሚል አቋም መያዛቸው ታውቋል።
ነባር ፓርቲ መሆናቸውን ጠቅሰው ላቀረቡት ልዩ ጥያቄ ” ከማንኛውም የክልልም ፓርቲ የተለየ የሚደረግ ነገር የለም። ነገር ግን ለተወሰነ ጊዜ ትህነግ የሚለውን ስም ያዝችሁ መቀጠል ትችላላችሁ” መባሉን ከዜናው ሰዎች መረጃ ለመረዳት ተችሏል።
ከወደ መቀለ የሚሰማውን ጉምጉምታ ጠቅሰው አዲስ አበባ የሚገኙ የትግራይ ተቀናቃኝ ፓርቲ አባል እንዳሉት በመጪው ምርጫ በትግራይ የፌደራል ፓርቲዎችን ጨምሮ በርካታ ድርጅቶች ይሳተፋሉ። አሁን ላይ ለትህነግ ራስ ምታት የሆነበት በትግራይ ይፋዊ የመድረክ ላይ ሙግት ሲጀመር ምላሽ መስጠትና መከራከር አለመቻሉ ነው። ምርጫውን የሚመራውም የፌደራሉ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ በመሆኑ እንደሚሸነፍ ግልጽ ነው። በመሆኑም አስቀድሞ ሌላ ዋስትና እንደፈለገ መስማታቸውን፣ ይህን ደግሞ መንግስት ውድቅ ማድረጉን እንደሚያውቁ አመልክተዋል።
“ብልጽግናን በይፋ ተቀላቅሎ ለህዝብ ማወጅ ለትህነግ የሞት ያህል ነው” የሚሉት የተቀናቃኝ ፓርቲው አመራር፣ ብቻውን ለመቀጠል ቢወስን እንደማይሳካለት ይገልጻሉ። ስለዚህም ትህነግ በሁለት የሞት ሸረት ውጥረት ውስጥ ይገኛል። ይህም ውጥረት ነው አቶ ጌታቸው በግመገማው ላይ ድል እንዳገኙ አስመስለው መግለጫ እንዲሰጡ ያስገደዳቸው።
እሳቸው ባላቸው መረጃ የትግራይ ህዝብ ከችግር መውጣት፣ ከተፈናቀለበት ስፍራ ተመልሶ ህይወቱን በሰላም መምራት እንጂ ካሁን በሁዋላ ጦርነት አይመኝም። ካለፈው ጦርነት በቂ ልምድ ያገኘው የትግራይ ህዝብ እንደቀድሞው አሁን በስሜት እንደማይነዳ አመልክተው ” ቀደም ሲል ልጆቻቸውን የደበቁ፣ ወደ አዲስ አበባ የላኩ አትርፈዋል። በስሜት ልጆቻቸውንም ሆነ ራሳቸውን የሰጡ ዛሬ አካል ጉዳተኛ፣ ሙትና በሽተኛ ሆነው ቀርተዋል። በትግራይ የሆነው ሁሉ ቤትና ወላድ ይቁጠሩት። ይህ ሁሉ የሆነው በትህነግ ስለሆነ ይህን ሁሉ ሃጢያቱን ተሸክሞ ወደ ምርጫ መግባት ስለማይቻለው ሌላ መከራ ለመደገስ ቢያቅድም አይህኖንም”
ዛሬ ለትግራይ ያለው አንድ ቋሚና አስተማማኝ መገናኛ አውሮፕላን ነው። ጦርነት መግባት ማለት አውሮፕላን፣ ስልክ፣ መብራት፣ መድሃኒት፣ … ሁሉም ይቆማል ማለት ነው። ያለፈው ስህተት እንደማይደገም እርግጠኛ ሆነው የሚናገሩት የክልሉ ተቀናቃኝ ፓርቲ አመራር፣ ትህነግ ከገባበት አጣብቂኝ መውጣት የሚችለው ብልጽግናን በመቀላቀል ብቻ እንደሆነ ይናገራሉ። አለያ በግል ተወዳድሮ ትግራይ ውስጥ ማሸነፍ አይችልም። ሰው ሁሉ አሁን ገብቶታል። ምርጫ ሲስደርስ ብዙ ሚስጢሮች ይፋ ይሆናሉ። የምርጫ ቅስቀሳውን የሚመራው ምርጫ ቦርድ ስለሆነ ማገድም፣ መገደብም ስለማይችል ፋይሉ ይገለጻል።
የምርጫ ቦርድ ዕውቅናን አስመልክቶ ጉዳዩ በህግ እንደሚታይ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ እንደተናገሩ፣ የዜናው ሰዎች አመልክተዋል። የአወዛጋቢ አካባቢዎችን አስመልክቶ ግን ” ሪፈረንደም” እንደ አንድ አማራጭ ቀረበ እንጂ መንግስት “ይህ መሆነ አለበት” አላለም። አቶ ጌታቸውም ሲናገሩ ” ዴሞግራፊውን ” ለማዛባት፣ የህዝብ ድምጽ ለማግነት ሲባል ህዝብ የማስፈር ስራ መሰራቱን እንደማይቀበሉ ከመናገራቸው ውጪ አማራጩ አንድና ብቸኛ ስለምሆኑ ያሉት ነገር የለም። ከአማራ ክልል በኩልም “እየተሰራበት ነው” ከማለት በዘለለ ዝርዝር አይባልበትም። በሁሉም ወገኖች የሚታመንበት ጉዳይ ግን የተፈናቀሉ ሰላማዊ ዜጎች ወደ ቀያቸው የመመለሳቸው ጉዳይ ነው።
የትግራይ ክልል ጊዚያዊ አስተዳደር መሪ አቶ ጌታቸው ከግምገማው በሁዋላ መቀለ ሲመለሱ በሰጡት መግለጫ የስራ ሪፖርት ሪፖርት ማቅረባቸውን አስታውቀው “በሚቀጥለው ወር መጋቢት የአፍሪካ ህብረት ፣ የተባበሩት መንግስታትና የአሜሪካ መንግስት ተወካዮች በተገኙት የፕሪቶሪያ ስምምነት አተገባበር ላይ ያተኮረ ውይይት ይካሄዳል ያሉት አቶ ጌታቸው የትግራይ ጊዚያዊ አስተዳደር ለውይይቱ ስኬት የበኩሉ አስተዋፅኦ ለማድረግ ዝግጁ ነው” ሲሉም መናገራቸው ይታወሳል።