1971 ላይ የካምፕ ዴቪድ ስምምነት ተፈረመ – በዚህም ግብፅ ለእስራኤል የሀገርነት ዕውቅ ሰጠች – የእስራኤል ባለሙያዎችም ‘ጣና በለስን’ ሳይውሉ ሳያድሩ ለቀው ወጡ…. አሁንም ቢሆን የካይሮ መንግስት ፍልስጤማዊያን ከጋዛ መሬት ሙሉ በሙሉ ተሰድደው መሬቱ ለእስራኤል ቢተላለፍ ከአልሲሲ ግላዊ አቋም አኳያ ወደ ኋላ እንደማይል፣ የቲራን እና ሳናፊር ደሴቶቻቸውን ለእስራኤል ስትራቴጂክ ፍላጎት መሟላት ለሳኡዲ ያስተላለፉበትን የቅርብ ጊዜ ውሳኔ ማውሳት በቂ ነው።
የዓባይ:ልጅ
~የግብፅ እና የእስራኤል ፍጥጫ፤ ካይሮ የካምፕ ዴቪድ የሰላም ስምምነትን እንደምታፈርስ ዛተች~
ከቅርብ ሳምንታት ወዲህ በተለይም ከካይሮ እስከ አንካራ፣ ከጋዛ እስከ አፍሪቃ ቀንድ ከሚስተዋሉ የአሰላለፍ መልኮች ጋር የሀገራት መሪዎችና የስለላ ኃላፊዎች ወደ ካይሮ ጉዞ የማድረጋቸው አንድምታ፣ ከጋዛ/ሐማስ ጉዳይ ባሻገር ኢትዮጵያ የባህር በር ለማግኘት በምታደርገው ጥረት ውስጥ ከፍተኛ ስንስል ያላቸው ቁማሮችም ይመስላሉ —። ሰሞነኛው የግብፅና እስራኤል ‘ታንቲራ’ የካምፕ ዴቪድ ስምምነትን መንካት መጀመሩ ይበልጥ ሀገራችንን የሚመለከት ያደርገዋል። ካይሮ በዚሁ የካምፕ ዴቪድ ስምምነት ወቅት ኢትዮጵያን የተመለከተው ይዘት ቁልፍ ሆኖ የተካተተ እንደነበርና በዚህም በሀገራችን የከፍታ ፕሮጀክቶች ላይ ጥቁር ጥላውን አሳርፎ ስለመቆየቱ የሚያወሳውን ታሪክ እዚጋ ልብ ይሏል…።
እስከ ትናንት ድረስ ከወጡ ዓለም አቀፍ ዘገባዎች ውስጥ አበይት የሆኑትን ብቻ ብንመለከት፤
▪️የእስራኤሉ መሪ ቤንያሚን ናታንያሁ በራፋህ ለሚደረገው ወታደራዊ ወረራ ለመዘጋጀት ተጠባባቂ ወታደሮቻቸው እንዲዘጋጁ ትዕዛዝ አስተላልፈዋል።
▪️ግብፅ ራፋ ላይ እስራኤል ያቀደችውን ጥቃት ፈፅሞ አልቀበለውም’ አለች።
▪️”ግብፅ በሰሜን ምስራቅ ሲና ከእስራኤል በሚያዋስናት ድንበር 40 ታንኮች እና ብረት ለበስ ወታደራዊ ተሽከርካሪዎቿን አሰማራች።”
▪️”የእስራኤል ጦር በጋዛ ድንበር ወደምትገኘው ራፋህ ከተማ የሚገፋ ከሆነ 45 አመት የዘለቀውን የካምፕ ዴቪድ ስምምነት እንደምትዘርዝ ግብፅ ዛቻ አሰማች”
▪️”ሳዑዲ እና UAE እስራኤል በራፋህ የምታደርገውን ዘመቻ በፍፁም እንደማይቀበሉትና አደገኛ መሆኑን አስታወቁ”
በዛሬው ዕለት ደግሞ ተከታዮቹ ክስተቶች ተስተውለዋል፦
▪️”ግብፅ የሚሳኤል መከላከያ ስርአቶችን ወደ ጋዛ ሰርጥ ድንበር እያንቀሳቀሰች ነው። በቅርብ ጊዜ ውስጥም የእስራኤል ወታደሮች እዚሁ ቦታ(ራፋህ አካባቢ) ሊታዩ ይችላሉ።
▪️”እስራኤል በራፋህ የአየር ድብደባ ጀመረች”
▪️”እስራኤል የራፋ ዘመቻዋን በተመለከተ ከምእራባዊያን የቀረበላትን ጥሪ ውድቅ አደረገች”
▪️”የ CIA ዋና ዳይሬክተር William J. Burns በነገው ዕለት ወደ ካይሮ ያቀናል።”
ዳይሬክተሩ ከቀናት በፊት (ጥር 18, 2024), ሞቃዲሾን ጎብኝተዋል። እስራኤልንም በተመሳሳይ..።
▪️”የቱርኩ መሪ ኤርዶኻን ከነገ በስቲያ ረቡዕ ካይሮን ሊጎበኙ ነው”
▪️”የሞሳድ ዳይሬክተር ዴቪድ ባርኒ ካይሮን ሊጎበኙ ነው። የኳታር ጠቅላይ ምኒስትርም በተመሳሳይ..።
.
. እዚህ ላይ ካይሮ የካምፕ ዴቪድ ካርድን እንደማስፈራሪያ መምዘዟ እስካሁን ድረስ ከ 26 ሺህ በላይ የፍልስጤማዊያን ህይወት ከተቀጠፈበት የጋዛ ቀውስ ብሎም ከሐማስ ጉዳይ ባሻገር ካይሮ አሁንም በፍልስጤማዊያን ህይወትና በሀገራችን ብሔራዊ ጥቅም ላይ የወጠነችው ሴራ መኖሩን በጉልህ የሚጠቁመን ክስተት ነው – ከካምፕ ዴቪድ የስምምነት ይዘት ውስጤ በተለይም ሀገራችንን የሚመለከተውን ነጥብ ማውሳት ተገቢ ይሆናል።
▪️የካምፕ ዴቪድ ሥምምነት በኢትዮጵያ ላይ፤
የእስራኤልን ምስረታ ተከትሎ በመካከለኛው ምስራቅ በተለይም ከግብፅ መንግስት ዕውቅና ይሰጣት ዘንድ የእስራኤል ዋነኛ አጋር የሆነችው አሜሪካ የካይሮን ስስ ብልት የሚነካ ካርድ መዘዘች…
ይኸውም በወንዛችን ዓባይ ውሃ ላይ ግድብ እንድንገነባ ለደርግ መንግስት ገፀበረከት የማቅረብ ‘አማላይ’ ቁማር ነበር። “በረሃብ የተቸገረ ህዝብህ በምግብ ራሱን እንዲችል ድጋፍ እናርግልህ፤ ወዳጅነታችንም ይበልጥ ይጠናከር” አሉት…
በመቀገል ወደ ‘ጣና በለስ’ የልኡካን ቡድን አሰማሩ፤ ማሽኖችን በመትከል እንቅስቃሴ ላይም እስራኤሎች መታየት ጀመሩ። ዋሽንግተን ፖስት እና ኒውዮርክ ታይምስ ጋዜጦችም ኢትዮጵያ በዓባይ ላይ ግድብ ለመገንባት ስራ ስለመጀመሯ አለም እንዲሰማው አደረጉ…
በመጨረሻም ለእስራኤል ዕውቅና ከልክሎ የቆየው የወቅቱ የግብፅ መሪ አንዋር ሳዳት አሜሪካን መማፀን ነበረበት “ግድቡን አስቁሚ” በማለት። ይህን ተከትሎ በተደረጉ ንግግሮች 1971 ላይ የካምፕ ዴቪድ ስምምነት ተፈረመ – በዚህም ግብፅ ለእስራኤል የሀገርነት ዕውቅ ሰጠች – የእስራኤል ባለሙያዎችም ‘ጣና በለስን’ ሳይውሉ ሳያድሩ ለቀው ወጡ…. አሁንም ቢሆን የካይሮ መንግስት ፍልስጤማዊያን ከጋዛ መሬት ሙሉ በሙሉ ተሰድደው መሬቱ ለእስራኤል ቢተላለፍ ከአልሲሲ ግላዊ አቋም አኳያ ወደ ኋላ እንደማይል፣ የቲራን እና ሳናፊር ደሴቶቻቸውን ለእስራኤል ስትራቴጂክ ፍላጎት መሟላት ለሳኡዲ ያስተላለፉበትን የቅርብ ጊዜ ውሳኔ ማውሳት በቂ ነው።
ይሁንና አልሲሲ ይህን ለመተግበር የአረብ አበዳሪ ሀገራት የሆኑት UAE, ሳዑዲ, ኳታርና ሌሎችም አይፈቅዱም፤ በሌላ ወገን ሐማስ እና ኢራን በከፋ ደረጃ የሚሳተፉበት ይሆናል።
ከሁሉም በላይ ግን ይህን ውሳኔ የአልሲሲ ካቤኔ በራሱ እንደማይቀበለው ነው የሚዘገበው። ይህም ግብፅ ከእስራኤል ጋር የከረረ ውጥረት ውስጥ እንዲቀጥሉ ሲያደርግ በአንፃሩ ደግሞ ኢትዮጵያ ከግብፅ የሚፃረር ስትራቴጂክ አጋር እንድታገኝ የሚያደርግ ይሆናል። በተለይም እስራኤል እና ግብፅ ከጦርነት በመለስ የሚፈጥሩት የዲፕሎማሲ መቆራቆሳቸውና እና ርስበርስ በስጋትና በጥርጣሬ እየተያዩ መቀጠላቸው ነው ለአዲስ አበባ የተሻለ ስትራቴጂክ ፋይዳ የሚያስገኘው(እንደሚመስለኝ)።
የሆነው ሆኖ ኢትዮጵያን ለማደናቀፍ ካይሮ ትላንት የተጠቀመችበት የቁማር ካርድ ለዛሬ የሚያገለግለበት ጂኦፓለቲካዊ ተጨባጭ በአንፃራዊነት የለም ሊባል ቢችልም፣ ጉዳዩን በአንክሮ መከታተልና በፍጥነት የሚለዋወጠውን ቀጣናዊ የብዝኃ ሀገራት ቁማር ታሳቢ ያደረገ ርተግባር ማከናወን የክቡር አምባሳደር ታዬ አፅቀ ሥላሴ ቁልፍ የቤት ስራ የሚሆንይመስላል…
ሠላም ለአለማችን!
Esleman Abay