ሩስያ ከኢትዮጵያ ጎን እንደምትቆምና ድጋፍ እንደምታደረግ አረጋገጠች

የሩስያ ውጭ ጉዳይ ሚንሥትር ሠርጌ ላቭሮቭ፦ የኢትዮጵያ መንግሥት ትግራይ ክልል ውስጥ የሰብአዊ ተግዳሮትን ለመወጣት የሚያደርገውን ጥረት የሩስያ ፌዴሬሽን ዕውቅና እንደሚሰጥ ገለጡ።

የሩስያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሰርጌይ ላቭሮቭ ይህን ያሉት ከኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ እና ምክትል ሚንሥትር ደመቀ መኮንን ጋር ትናንት በስልክ ከተወያዩ በኋላ ነው። በውይይቱ ወቅትም አቶ ደመቀ በትግራይ ክልል ውስጥ ስላለው መልሶ ግንባታ እና ማቋቋም ለሠርጌ ላቭሮቭ ማብራራታቸው ተጠቊሟል።

ትግራይ ውስጥ የሰብአዊ ድጋፍ ኹኔታ ስኬታማ በሆነ መልኩ መቀጠሉን ማብራራታቸውንም ውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት ገልጧል። ሠርጌ ላቭሮቭ የኢትዮጵያ መንግሥት ትግራይ ክልል ውስጥ ያለውን የሰብአዊ ተግዳሮትን በተመለከተ የሚያደርገውን ጥረት እንደሚረዱ መንግሥታቸውም በዚህ ጉዳይ ኢትዮጵያን መርዳቱን ለመቀጠል ምንጊዜም ዝግጁ መሆኑን ጠቊመዋል።

ሩስያ አባል የሆነችበት የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የፀጥታው ጥበቃ ምክር ቤት ባለፈው ሳምንት በትግራይ ጉዳይ በዝግ መምከሩ የሚታወስ ነው።

በሌላ ዜና ፋና እንዳለው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እና ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት የልማት ፕሮግራም ምክትል አስተዳዳሪ እና የአፍሪካ ቀጠና ሃላፊ አሁና ኢዚኮኖዋ ጋር ተወያዩ፡፡

በውይይታቸው ወቅትም በትግራይ ክልል ስላለው የሰብአዊ እርዳታ ሁኔታ፣ በኢትዮጵያ እና በድርጅቱ መካከል ስላለው ትብብር እና በመጭው ሃገር አቀፍ ምርጫ ዙሪያ መክረዋል፡፡

የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ የተመድ የልማት ፕሮግራም ኢትዮጵያ የ2030 ዘለቂ የልማት ግቦችን ለማሳካት ለምታደርገው ጥረት የሚያደርገውን ድጋፍ አድንቀዋል፡፡

አያይዘውም በኢትዮጵያ እየተካሄደ ስላለው ሃገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ ፕሮግራምና ኮቪድ19 ዘላቂ የልማት ግቦችን ለማሳካት በሚደረገው ጥረት ላይ ያሳደረውን ተፅዕኖ በተመለከተ ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡

ከትግራይ ክልል ጋር በተያያዘ በሰጡት ማብራሪያም መንግስት አሁን ላይ በህግ ማስከበር ዘመቻው ወቅት ለተጎዱ ዜጎች ሰብአዊ ድጋፍ ማድረግ፣ መልሶ ማቋቋምና በህወሓት ጉዳት የደረሰባቸውን መሰረተ ልማቶች መልሶ ግንባታ ላይ ትኩረት ማድረጉን አስረድተዋል፡፡

አያይዘውም መንግስት በትግራይ ክልል 92 የእርዳታ ማሰራጫ ጣቢያዎችን በማቋቋም ከተመድ እና ሌሎች ረጂ ድርጅቶች ጋር በቅንጅት እየሰራ ነው ብለዋል፡፡

See also  ሠራዊቱ ዝግጁነቱን አረጋግጦ ይገኛልየህዳሴ ግድባችን ሕልውናችንና የሕዝባችን አንጡራ ሃብት...

የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የልማት ፕሮግራም ምክትል አስተዳዳሪ እና የአፍሪካ ቀጠና ሃላፊ አሁና ኢዚኮኖዋ በበኩላቸው ከመጭው ሃገራዊ ምርጫ ጋር በተያያዘ ድርጅቱ ተአማኒ፣ አካታች እና ሰላማዊ ምርጫ እንዲደረግ የቦርዱን አቅም ለማጠናከር የጀመረውን ፕሮግራም ተግባራዊ እንደሚያደርገው ገልጸዋል።

የተመድ የልማት ድርጅት ለኢትዮጵያ ልማት የሚያደርገውን ድጋፍ ይቀጥላልም ነው ያሉት። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የልማት ፕሮግራም ምክትል አስተዳዳሪ እና የአፍሪካ ቀጠና ሃላፊ አሁና ኢዚኮኖዋ በኢትዮጵያ የስራ ጉብኝት እያደረጉ ሲሆን፥ ከመንግስት ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች ጋር ይወያያሉ ተብሎ ይጠበቃል።

    Leave a Reply