የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር መሪ አቶ ጌታቸው ረዳ የፌዴራል መንግሥቱና ዓለም አቀፉ ማሕበረሰብ በክልሉ የተከሰተውን ድርቅ ለመግታት እጃቸውን እንዲዘረጉ በማሕበራዊ ሚድያ ገፃቸው ባሰራጩት መግለጫ ጠየቁ። በክልሉ ያለው ድርቅ እጅግ አሳሳቢ ደረጃ መድረሱን አመልክተዋል።
“በትግራይ ረሃብ እና ሞት እያንዣበበ ነው” ሲሉ የገለጡት አቶ ጊታቸው ችግሩ ከ1977 በኋላ ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ እጅግ የከፋ ድርቅ ብለዋታል። ርዕሰ መስተዳድሩ አክለው አሁን የተከሰተው ድርቅና በትግራይ የነበረው ደም አፋሳሽ ጦርነት ተደማምረው ከፍተኛ አደጋ ሊያደርሱ እንደሚችሉ ጠቁመዋል።
የትግራይ ኢኮኖሚ መቃወስ፤ የክልሉ መሠረት ልማቶች በተለይ የጤና ተቋማት መውደማቸው እና በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች ከቤት ንብረታቸው መፈናቀላቸው የትግራይ ክልል ነዋሪዎችን ለከፍ ችግር ማጋለጡን አቶ ጌታቸውን በመግለጫቸው አውስተዋል።
“ስለዚህ ጊዜያዊ አስተዳደሩ የፌዴራል መንግሥትና ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ በትግራይ እያንዣበበ ያለውን ረሃብና ሞት ለመታደግ ሕጋዊ እና ሞራላዊ ግዴታቸውን ሊወጡ ይገባል” ብለዋል።
“ረሃብ ድምፅ አልባ ገዳይ መሣሪያ ነው” የሚሉት አቶ ጌታቸው የፌዴራል መንግሥቱና ዓለም አቀፉ ማሕበረሰብ “ይህን ገዳይ መሣሪያ ለማጥፋት” የበኩላቸውን አድርገዋል ሲሉ ያክላሉ።
“አሁን ደግሞ እያንዣበበ ያለውን ሰብዓዊ ቀውስ ለመግታት የበኩላቸውን ሊወጡ ይገባል” ሲሉ ጥሪያቸውን አቅርበዋል። ርዕሰ መስተዳድሩ በመግለጫቸው ማዕከላዊው መንግሥቱም ሆነ ሌሎች አካላት አፋጣኝ ምላሽ መስጠት እንዳለባቸው አስምረዋል።
የተጠበቀ ዝናብ ሳይዘንብ መቅረቱ፣ የአንበጣ ወረርሽኝ፣ ሰብዓዊ እርዳታ ለተወሰነ ጊዜ ያክል ተቋርጦ መቆየቱ አሁን ለተከሰተው ሰብዓዊ ቀውስ ምክንያት መሆኑን የጠቀሱት አቶ ጌታቸው እርዳታው በተወሰነ መልኩ ቢመለስም በቂ አለመሆኑን ጠቅሰዋል።
የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ይህን ሰብዓዊ ቀውስ ለመቀልበስ የበኩሉን ድርሻ እየተወጣ መቆየቱን የገለጡት ፕሬዝደንቱ ነገር ግን ሁኔታው ከጊዜያዊ አስተዳደሩ አቅም ውጭ መሆኑን አሳውቀዋል።
ጊዜያዊ አስተዳደሩ ከወሰዳቸው እርምጃዎች መካከል ሰብዓዊ ቀውሱን ለመግታት 50 ሚሊዮን ብር መመደብ አንዱ መሆኑን በመግለጫቸው ያነሱት ርዕሰ መስተዳድሩ ይህ የገንዘብ መጠን ከችግሩ አኳያ አነስተኛ መሆኑን ገልጠዋል ሲል የዘገበው ቢቢሲ ነው።